ሁሉም የእስልምና ቤተ መጻሕፍት

56 - The Inevitable - Al-Wāqi`ah

:1

መከራይቱ በወደቀች ጊዜ፡፡

:2

ለመውደቋ አስተባባይ (ነፍስ) የለችም፡፡

:3

ዝቅ አድራጊና ከፍ አድራጊ ናት፡፡

:4

ምድር መናወጥን በተናወጠች ጊዜ፡፡

:5

ተራራዎችም መፍፈርፈርን በተፈረፈሩ ጊዜ (እንደተፈጨ ዱቄት በኾኑ ጊዜ)፡፡

:6

የተበተነ ብናኝ በኾኑም ጊዜ

:7

ሦስት ዓይነቶችም በኾናችሁ ጊዜ (ታዋርዳለች፤ ታነሳለችም)፡፡

:8

የቀኝ ጓዶችም ምን (የተከበሩ) የቀኝ ጓዶች ናቸው፡፡

:9

የግራ ጓዶችም ምን (የተዋረዱ) የግራ ጓዶች ናቸው፡፡

:10

(ለበጎ ሥራ) ቀዳሚዎቹም (ለገነት) ቀዳሚዎች ናቸው፡፡

:11

እነዚያ ባለሟሎቹ ናቸው፡፡

:12

በመጠቀሚያ ገነቶች ውስጥ ሲኾኑ፡፡

:13

ከፊተኞቹ ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡

:14

ከኋለኞቹም ጥቂቶች ናቸው፡፡

:15

በተታቱ አልጋዎች ላይ ይኾናሉ፡፡

:16

በእርሷ ላይ የተመቻቹና ፊት ለፊት የተቅጣጩ ሲኾኑ፡፡

:17

በእነርሱ ላይ ሁል ጊዜ የማያረጁ ወጣቶች ልጆች ይዘዋወራሉ፡፡

:18

ከጠጅ ምንጭም በብርጭቆዎችና በኩስኩስቶች በጽዋም (በእነርሱ ላይ ይዝዞራሉ)፡፡

:19

ከእርሷ የራስ ምታት አያገኛቸውም፤ አይሰክሩምም፡፡

:20

ከሚመርጡትም ዓይነት በእሸቶች፡፡

:21

ከሚሹትም በኾነ የበራሪ ሥጋ (ይዞሩባቸዋል)፡፡

:22

ዓይናማዎች የኾኑ ነጫጭ ቆንጆዎችም አሏቸው፡፡

:23

ልክ እንደተሸፈነ ሉል መሰሎች የኾኑ፡፡

:24

በዚያ ይሠሩት በነበሩት ምክንያት ዋጋ ይኾን ዘንድ (ይህንን አደረግንላቸው)፡፡

:25

በውስጥዋ ውድቅ ንግግርንና መውወንጀልን አይሰሙም፡፡

:26

ግን ሰላም መባባልን (ይሰማሉ)፡፡

:27

የቀኝም ጓዶች ምንኛ (የከበሩ) የቀኝ ጓዶች!

:28

በተቀፈቀፈ (እሾህ በሌለው) ቁርቁራ ውስጥ ናቸው፡፡

:29

(ፍሬው) በተነባበረ በሙዝ ዛፍም፡፡

:30

በተዘረጋ ጥላ ሥርም፡፡

:31

በሚንቧቧ ውሃ አጠገብም፡፡

:32

ብዙ (ዓይነት) በኾኑ ፍራፍሬዎችም፡፡

:33

የማትቋረጥም የማትከለከልም የኾነች፡፡

:34

ከፍ በተደረጉ ምንጣፎችም (ሴቶችም መካከል)፡፡

:35

እኛ አዲስ ፍጥረት አድርገን (ለእነርሱ) ፈጠርናቸው፡፡

:36

ደናግሎችም አደረግናቸው፡፡

:37

ለባሎቻቸው ተሽሞርሟሪዎች እኩያዎች (አደረግናቸው)፡፡

:38

ለቀኝ ጓዶች (አዘጋጀናቸው)፡፡

:39

ከፊተኞቹ ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡

:40

ከኋለኞቹም ብዙ ጭፍሮች ናቸው፡፡

:41

የግራ ጓደኞችም ምንኛ (የተዋረዱ) የግራ ጓዶች! ናቸው፡፡

:42

በመርዛም ነፋስ በጣም በፈላ ውሃም ውስጥ ናቸው፡፡

:43

ከጥቁር ጭስም በኾነ ጥላ ውስጥ፡፡

:44

ቀዝቃዛም መልካምም ያልኾነ፡፡

:45

እነርሱ ከዚህ በፊት ቅምጥሎች ነበሩና፡፡

:46

በታላቅ ኀጢአትም ላይ ይዘወትሩ ነበሩና፡፡

:47

ይሉም ነበሩ፡- «በሞትንና ዐፈር፣ ዐጥንቶችም በኾን ጊዜ እኛ በእርግጥ የምንቀሰቀስ ነን?

:48

«የፊተኞቹ አባቶቻችንም?»

:49

በላቸው፡- «ፊተኞቹም ኋለኞቹም፡፡

:50

«በተወሰነ ቀን ቀጠሮ በእርግጥ ተሰብሳቢዎች ናቸው፡፡

:51

«ከዚያም እናንተ ጠማሞች አስተባባዮች ሆይ!

:52

« ከዘቁም ዛፍ በእርግጥ በይዎች ናችሁ፡፡

:53

«ከእርሷም ሆዶቻችሁን ሞይዎች ናችሁ፡፡

:54

«በእርሱ ላይም ከፈላ ውሃ ጠጪዎች ናችሁ፡፡

:55

«የተጠሙንም ግመሎች አጠጣጥ ብጤ ጠጪዎች ናችሁ፡፡»

:56

ይህ በፍርዱ ቀን መስተንግዷቸው ነው፡፡

:57

እኛ ፈጠርናችሁ አታምኑምን?

:58

(በማኅፀኖች) የምታፈሱትን አያችሁን?

:59

እናንተ ትፈጥሩታላችሁን? ወይስ እኛ ፈጣሪዎቹን ነን?

:60

እኛ ሞትን (ጊዜውን) በመካከላችሁ ወሰንን፡፡ እኛም ተሸናፊዎች አይደለንም፡፡

:61

ብጤዎቻችሁን በመለወጥና በዚያ በማታውቁትም (ቅርጽ) እናንተን በመፍጠር ላይ (አንሸነፍም)፡፡

:62

የፊተኛይቱንም አፈጣጠር በእርግጥ ዐውቃችኋል፡፡ አትገነዘቡምን?

:63

የምትዘሩትንም አያችሁን?

:64

እናንተ ታበቅሉታላችሁን? ወይስ እኛ አብቃዮቹ ነን?

:65

ብነሻ ኖሮ ደረቅ ስብርብር ባደረግነውና የምትደነቁም በኾናችሁ ነበር፡፡

:66

«እኛ በዕዳ ተያዦች ነን፡፡

:67

«በእርግጥም እኛ (ከመጠቀም) የተከለከልን ነን» (ትሉ ነበር)፡፡

:68

ያንንም የምትጠጡትን ውሃ አየችሁን?

:69

እናንተ ከደመናው አወረዳችሁትን? ወይስ እኛ አውራጆቹ ነን?

:70

ብንሻ ኖሮ መርጋጋ ባደረግነው ነበር፡፡ አታመሰግኑምን?

:71

ያቺንም የምትሰብቋትን እሳት አያችሁን?

:72

እናንተ ዛፏን ፈጠራችሁን? ወይስ እኛ ፈጣሪዎችዋ ነን?

:73

እኛ (ለገሀናም) ማስታወሻ ለመንገደኞችም መጠቀሚያ አደረግናት፡፡

:74

የታላቁን ጌታህንም ስም አወድስ፡፡

:75

በከዋክብትም መጥለቂያዎች እምላለሁ፡፡

:76

እርሱም ብታወቁ ታላቅ መሓላ ነው፡፡

:77

እርሱ የከበረ ቁርኣን ነው፡፡

:78

በተጠበቀ መጽሐፍ ውስጥ ነው፡፡

:79

የተጥራሩት እንጅ ሌላ አይነካውም፡፡

:80

ከዓለማት ጌታ የተወረደ ነው፡፡

:81

በዚህ ንግግር እናንተ ቸልተኞች ናችሁን?

:82

ሲሳያችሁንም (ዝናምን) እናንተ የምታስተባብሉት ታደርጋላችሁን?

:83

(ነፍስ) ጉረሮንም በደረሰች ጊዜ፡፡

:84

እናንተ ያን ጊዜ የምታዩ ስትኾኑ፡፡

:85

እኛም ግን አታዩም እንጅ ከእናንተ ይልቅ ወደእርሱ የቀረብን ስንኾን፡፡

:86

የማትዳኙም ከኾናችሁ፡፡

:87

እውነተኞች እንደ ኾናችሁ (ነፍሲቱን ወደ አካሉ) ለምን አትመልሷትም፡፡

:88

(ሟቹ) ከባለሟሎቹ ቢኾንማ፡፡

:89

(ለእርሱ) ዕረፍት፣ መልካም ሲሳይም፣ የመጠቀሚያ ገነትም አልለው፡፡

:90

ከቀኝ ጓዶችም ቢኾንማ፡፡

:91

ከቀኝ ጓዶች ስለ ኾንክ ላንተ ሰላም አልለህ (ይባላል)፡፡

:92

ከሚያስዋሹት ጠማማዎችም ቢኾንማ፡፡

:93

ከፈላ ውሃ የኾነ መስተንግዶ አልለው፡፡

:94

በገሀነም መቃጠልም (አልለው)፡፡

:95

ይህ እርሱ እርግጠኛ እውነት ነው፡፡

:96

የታላቁንም ጌታህን ስም አወድስ፡፡